ቢዝነስዜናፖለቲካ

ዜና: አየር መንገዱ ወደ አስመራ “በረራ ያቋረጥኩት በሀገሪቱ የሚገኘው የባንክ ተንቀሳቃሽ ሂሳብ ደብተሬ በመታገዱ ነው” ሲል ገለጸ

አዲስ አበባ፣ ነሃሴ 28/2016 ዓ.ም፡- የኢትዮጵያ አየር መንገድ አስመራ ቅርንጫፍ የሂሳብ ደብተር ሙሉ ለሙሉ መታገዱ ወደ ኤርትራ የሚያደርገውን በረራ እንዲያቆም ካሰገደዱት መክንያቶች አንዱ መሆኑን ዋና ስራ አስፈፃሚው አቶ መስፍን ጣሰው ዛሬ ነሃሴ 28 ቀን 2016 ዓ.ም በሰጡት መገለጫ አስታውቀዋል።

ባለፉት ስድስት አመታት ወደ አስመራ ስናደርገው በነበረው በረራ የተቀላጠፈ አገረልግሎት ስንሰጥ ነበር ሲሉ የተደመጡት ዋና ስራ አስፈጻሚው በዚህም ሳቢያ በርካታ ደንበኞች ማፍራቱነ እና በቀን ሁለት በረራ ወደ አስመራ ያካሂድ እንደነበር ጠቁመዋል።

ከቅርብ ግዜያት ወዲህ ግን አየር መንገዱ በኤርትራ በኩል ይህንን ሁኔታ እንዳያስቀጥል የሚያደርግ ችግር እንደተፈጠረበት አመላክተዋል።

የኤርትራ ሲቪል አሺዬሽን ባለስልጣን በመጋቢት ወር 2016 ዓ.ም በመጻፈው ደብዳቤ “የብዙ ኤርትራውያን ተጓዦች የጠፉ ሻንጣዎች አሉ” በሚል የካሳ ክፍያ መጠየቁን አስታውሰው አየር መንገዱ ጠፉ የተባሉትን ሻንጣዎች በተመለከተ ስም እና የሻንጣ ቁጥር እንዲገለጽለት ቢጠይቅም ምንም የቀረበለን ዝርዝር የለም ሲሉ ገልጸዋል። የደንበኞች ሻንጣ መዘግየትን በተመለከተ ደግሙ የተለየ ነገር አይደለም ሲሉ አስታውቀዋል።

በተመሳሳይ ደብዳቤ በረራችንን በሳምንት ከ14 ወደ 10 እንድንቀንስ ተጠየቅን ሲሉ የገለጹት ስራ አስፈጻሚው በመግለጫቸው በተጨማሪም ለበረራ ትንንሽ አይሮፕላኖችን ብቻ ለመጠቀም ወስነን ነበር ብለዋል።

በሰኔ ወር 2016 ዓ.ም አየር መንገዱ በረራውን በሳምንት ወደ 15 ከፍ እንዲያደርግ እና ትላልቅ አውሮፕላኖችን እንዲጠቀም የሚፈቅድ ደብዳቤ ተጽፎለት እንደነበርም አስታውቀዋል።

በዚህም በተደጋጋሚ ከኤርትራ ሲቪል አሺዬሽን ሲነሱ የነበሩ ቅሬታዎችን ከመፍታት ጀምሮ ዕለታዊ የበረራ ቁጥርንም በመጨመር ሳምንትታዊ የበረራ መጠኑ ወደ 15 አድጎ እንደነበር ጠቁመዋል።

Download the First Edition of Our Quarterly Journal

ከዚህ ቀደም የኤርትራ ሲቪል አቪዬሽን ከመንገደኞች ሻንጣ መዘግየት ጋር ተያይዞ ያለውን ችግር ለመፍታት 160 መቀመጫ ባለው አውሮፕላን 100 መንገደኞችን ይዞ እንዲበር መደረጉን ገልፀዋል።

በሐምሌ ወር ከኤርትራ ሲቪል አቬሽን በተጻፈ ደብዳቤ ከመስከረመ ወር 2017 ዓ.ም በኋላ ወደ ኤርትራ ምንም አይነት በረራ እንዳናደርገ የሚያሳውቅ ደብዳቤ ተጻፈ ሲሉ አውስተዋል።

በተጨማሪም ደብዳቤው በኤርትራ ሲቪል አቪዬሽን በኩል መውጣቱን ተከትሎ በኢትዮጵያ ሲቪል አቪዬሽን በኩል በደብዳቤና በስልክ ተደጋጋሚ ሙከራዎች ቢደረጉም ምላሽ ማግኘት እንዳልተቻለ ገልጸዋል።

ችግሩን ለመፍታት እና መፍትሄዎችን ከማፈላለግ ጎን ለጎን በረራዎችን ሲደረጉ መቆየታቸውን ጠቅሰዋል።

በዚህ መሃል በኤርትራ የኢትዮጵያ አየር መንገድ ተወካይ ገንዘብ ለማስቀመጥ ወደ ባንክ ባቀናበት ጊዜ ገንዘብ ማስቀመጥ እንደማይችል በኤርትራ ሲቪል አቪዬሽን ባለስልጣን በተፃፈ ደብዳቤ መታገዱን ባንኩ እንደገለጸላቸው አመላክተዋል።

አየር መንገዱ ይህን ውሳኔ ከሰማበት ጊዜ ጀምሮ ምላሽ ለማግኘት የተለያዩ ጥረቶችን ሲያደርግ ቢቆይም ምላሽ ማግኘት እንዳልቻለም አስረድተዋል።

ያለ ፍርድ ቤት ትዕዛዝ የአየር መንገዱ የሂሳብ ደብተሩ መዘጋት እንደማይቻል በደብዳቤ ጭምር ቢያሳውቅም ባንኩ የተላለፈውን ውሳኔ መቀየር እንደማይችል ገልፆልናል ብለዋል።

አየር መንገዱ ለሰራተኞቹና ለተለያዩ አገልግሎቶች ክፍያዎችን መፈፀም ባለመቻሉ በረራውን ለመሰረዝ መገደዱን ተናግረዋል።

የኢትዮጵያ አየር መንገድ ከነሐሴ 28 ቀን ጀመሮ ወደ አስመራ ምንም አይነት በረራ እንደማይኖረኝ እወቁልኝ ማለቱን መዘገባችን ይታወሳል። አስ

ተጨማሪ አሳይ

ተዛማጅ ጽሑፎች

Back to top button