ቢዝነስዜናፖለቲካ
በመታየት ላይ ያለ

ዜና፡ መንግስት በአማራ እና ኦሮሚያ ክልሎች ከሚንቀሳቀሱ የታጠቁ ኃይሎች ጋር “በሚስጥር” ንግግር እያደረገ መሆኑን ጠ/ሚ አብይ አህመድ ገለጹ

አዲስ አበባ፣ ሐምሌ 26/ 2016 ዓ/ም፦ መንግስት በአማራ እና ኦሮሚያ ክልል ከሚንቀሳቀሱ የታጠቁ ኃይሎች ጋር በሚስጥር ንግግር እያደረገ መሆኑን ጠ/ሚ አብይ አህመድ (ዶ/ር) ገለጹ። 

ጠ/ሚ አብይ አህመድ በቅርቡ ተግባራዊ የተደረገውን የማክሮ ኢኮኖሚ ማሻሻያን በተመለከተ በሰጡት ማብራሪያ፤ ማሻሻያውን ውጤታማ ለማድረግ ሰላምና መረጋጋት ወሳኝ መሆኑን ጠቅሰዋል። 

በዚህም መሰረት በአማራ ከሚንቀሳቀሱ ከተወሰኑ የታጠቁ ኃይሎች ጋር ንግግር ከተጀመረ ውሎ ማደሩን ገልጸዋል። ጠ/ሚ ከታጣቂዎቹ ጋር እየተደረገ ያለው ንግግር አስቸጋሪ ያደረገው ኃይሉ አንድ አለመሆኑ ጠቅሰው አንድ እንዲሆኑ ከፍተኛ ጥረት ሲደረግ ነበር ብለዋል። 

በተመሳሳይ መልኩ  “ሸኔ” ሲሉ ከጠሩት በኦሮሚያ ክልል የሚንቀሳቀሰው የኦሮሞ ነጻነት ሰራዊት አንድ አለመሆናቸውን ጠቅሰው ከተወሰኑት ጋር ቀጣይነት ያለው ንግግር እያደረን ነው ብለዋል። 

ጠቅላይ ሚኒስትሩ “ከታጣቂዎቹ ጋር እየተደረጉ ያሉት ንግግሮች ፍሬያማ እንዳይሆን ያደረገው ጉዳይ በአንድ ስም የሚጠሩ በጣም ብዙ ኃይሎች ያሉበት ስለሆነ ከአንደኛው ጋር መግባባት ሙሉ ውጤት ላያመጣ ይችላል። ግን አንድ በአንድ የዚህ ነገር መቋጫ ሰላም ነው” ሲሉ ገልጸዋል። 

አብይ በማብራሪያቸው የማክሮ ኢኮኖሚ ማሻሻያ ለአገሪቱ ኦኮኖሚ ጠቃሚ መሆኑን ገልጸው ለስኬታማነቱ የጋራ ጥረቶች እንዲደረጉ ጥሪ አቅርበዋል።

“የእነዚህ ማሽሻያ ስኬት ወይም ውድቀት በእኛ እጅ ነው፤ እኛ ነን የምንወስነው” ያሉት ጠ/ሚሩ አርሶ አደሮች፣ ላኪዎችና መንግስት በጋራ እንዲሰሩ አሳስበዋል። “ገቢ መጨመር አለበት፣ ኤክስፖርት መጨመር አለበት፣ ምርትም መጨመር አለበት፤ ይህ ካልሆነ ግን ማሻሻያው አደጋ ላይ ይወድቃል” ብለዋል።

Download the First Edition of Our Quarterly Journal

“ማሻሻያው አገራዊ ለውጡን ተከትሎ እየተተገበረ ያለውን በመደመር እሳቤ የልማት ጽንሰ ሃሳብ መርሆችን መሰረት ያደረገ” መሆኑን አብራርተዋል፡፡ መንግስት ከወሰናቸው ውሳኔዎች መካከል አንደኛው የኢትዮጵያን ኢኮኖሚ ለግሉ ዘርፉ ተሳትፎ ክፍት ማድረግ እንደነበርም አስታውሰዋል፡፡

ከዛ በኋላ ባሉ ሂደቶችም በተለይ በመጀመሪያ የሀገር በቀል ኢኮኖሚ ማሻሻያ አማካኝነት በተወሰነ መልኩ ኢኮኖሚውን ለግሉ ሴክተር ተሳትፎ ነጻ የማድረግ ስራ መከናወኑን አንስተው፤ ከዚህ አኳያ የማክሮ ኢኮኖሚ ማሻሻያው አዲስ ጉዳይ አለመሆኑን ተናግረዋል፡፡

በአፍሪካ ግዙፍ ኢኮኖሚ ከገነቡ አገራት መካከል የኢትዮጵያ ኢኮኖሚ ብቻ በበርካታ ጉዳዮች ዝግ እንደነበር የጠቀሱት ጠቅላይ ሚኒስትሩ፤ አሁን ላይ ባለው ነባራዊ ሁኔታ በዚህ መንገድ ኢኮኖሚውን አስቀጥሎ ውጤታማ ማድረግ አይቻልም ብለዋል፡፡

ኢትዮጵያ የራሷን ኢኮኖሚ ዘግታ የአፍሪካ የንግድ ቀጠናን ጨምሮ በዓለም አቀፍ ገበያ ተጠቃሚ መሆን እንደማትችልም ነው አጽኖት ሰጥተው ያብራሩት፡፡

ኢትዮጵያ በተለይ በአህጉር አቀፍ ደረጃ ተግባራዊ በሚደረገው የአፍሪካ ነጻ የንግድ ቀጠና ተጠቃሚ ለመሆን የተዘጋው ኢኮኖሚ ክፍት መደረግ እንዳለበት ገልጸው፤ ማሻሻያውም ይህን ተግባራዊ የሚያደርግ መሆኑን አብራርተዋል፡፡

በተጨማሪም መንግስት በዋናነት ዝቅተኛ ገቢ ለላቸው የመንግስት ሰራተኞች ማለትም 1,500 ብር የሚከፈላቸው ሰራተኞችን ደመወዝ በ300 ፐርሰንት ሊጨምር መሆኑን ገልጸዋል።  ለደመወዝ ጭማሪው ከ90 ቢሊዮን ብር በላይ እንደመደበም ጠቅሰዋል።

ጠቅላይ ሚኒስትሩ በጥቁር ገበያ እና በባንኮች የምንዛሬ ተመኖች መካከል ያለውን ልዩነት ማጥበብ አስፈላጊ መሆኑን አፅንዖት ሰጥተዋል። የዶላር ዋጋ መጨመርን ተከትሎ አላስፈላጊ ዋጋ ጭማሪ የሚደርጉ አካላት ላይ የተቀናጀ እርመጃ እንደሚወሰድ አስታወቀዋል።

ጠቅላይ ሚኒስትር አብይ በማብራሪያቸው የኢኮኖሚ ማሻሻያው ፈታኝ ሊሆን እንደሚችል ጠቁመዋል። ” የ2017 በጀት ዓመት ከባድ ጊዜ ነው፤ ያንገጫግጨናል፤ መዘጋጀት ያስፈልጋል” በማለት ተናግረዋል። አስ

  

ተጨማሪ አሳይ

ተዛማጅ ጽሑፎች

Back to top button