አዲስ አበባ፣ መስከረም 9/ 2016 ዓ.ም፡- በሸገር ከተማ ገላን ክፍለ ከተማ ውስጥ የሚገኘው ጊዜያዊ ማቆያ ማእከል ውስጥ በተከሰተው በተባይ የሚተላለፍ ሕመም ሶስት ሰዎች መሞታቸውን የኢትዮጵያ ሰብአዊ መብቶች ኮሚሽን (ኢሰመኮ) አስታወቀ፡፡
የኢትዮጵያ ሰብአዊ መብቶች ኮሚሽን ይህን ያለው ከጎዳና ላይ ተነስተው በማቆያ ማዕከል ውስጥ እንዲቆዩ የሚደረጉ ሰዎችን በተመለከተ ትላንት ባወጣው መግለጫ ነው፡፡
በሸገር ከተማ፣ ሲዳ አዋሽ ወረዳ በተለምዶ “ሲዳሞ አዋሽ” በመባል የሚታወቅ አካባቢ የሚገኘው ጊዜያዊ ማቆያ ማእከል ከነበሩ በተከሰተው በሽታ ተጨማሪ ሶስት ሰዎች በጽኑ ሕሙማን ክፍል ውስጥ ሕክምና እያገኙ እንደነበር ገልጧል፡፡
በማቆያ ቦታው የተከሰተው ተላላፊ በሽታ በተባይ (በቅማል) የሚመጣ የተስቦ በሽታ (Relapsing fever) መሆኑን የገለጸው ኮሚሽኑ በመጠለያ ጣቢያው ከነበሩ ሰዎች መካከል 190 ሰዎች በሆስፒታል የሕክምና አገልግሎት ያገኙ መሆኑን ገልጧል፡፡
ኮሚሽኑ በመግለጫው በሺዎች የሚገመቱ ውሎ እና አዳራቸውን በጎዳና ላይ ያደረጉ ሰዎች በማቆያ ማእከሉ ውስጥ ይገኙ እንደነበር ጠቅሶ አረጋውያን፣ ሕፃናት፣ ሴቶች እና አካል ጉዳተኞችም ይገኙበታል ብሏል፡፡
ኢሰመኮ ወደ ማቆያ ማእከሉ እንዲገቡ በሚደረጉ ሰዎች ላይ የግዳጅ አሠራር በአፋጣኝ ከማስቆም በተጨማሪ ለችግሩ ዘለቄታዊ እና ሁሉን አቀፍ የፖሊሲ ምላሽ ይሻል ነው ያለው፡፡
የአዲስ አበባ ከተማ አስተዳደርን ጨምሮ የሚመለከታቸው የከተማ የጸጥታ እና አስተዳደር አካላት በአሁኑ ወቅት በዚህ ማቆያ ማእከል የሚገኙ ሰዎችን አያያዝ ለማሻሻልና ሰብአዊ ክብርና አያያዝን ለማረጋገጥ የሚያስችል በቂ የምግብ፣ የውሃ፣ የመኝታ፣ የንጽሕና እና የሕክምና አገልግሎቶችን በአፋጣኝ ሊሟሉ ይገባል ሲልም አሳስቧል።
ኢሰመኮ በመግለጫው ሰዎችን በግዳጅ ወደ አንድ ማቆያ ማእከል/ቦታ ማስገባት ወይም ለኑሮ ከመረጡት ቦታ ወደ ማይፈልጉበት አካባቢ እንዲሄዱ ማስገደድ የሰብአዊ መብቶች ጥሰት የሚያስከትል በመሆኑ፤ ይህ አስገዳጅ አሠራር በአስቸኳይ እንዲቆም በማድረግ በጎዳና ላይ ያሉ ሰዎችን ከጎዳና ላይ ማንሳትና ተገቢ አገልግሎቶችን መስጠት በፈቃደኝነትና አስፈላጊ ሁኔታዎችን ሁሉ በማመቻቸት ሊተገበር የሚገባ በመሆኑ በአስቸኳይ የእርምት እርምጃዎችን መውሰድ ያስፈልጋል ብሏል።አስ