አዲስ አበባ፣ ጥቅምት 1/ 2017 ዓ/ም፦ ግብፅ፣ ሶማሊያ እና ኤርትራ ባደረጉት የሶስትዮች ጉባዔ፤ ሶማሊያ የየብስ እና የባህር ድንበሮቿን ለመጠበቅ የሚያስችላትን አቅም ለማጠናከር በሚወሰዱ እርምጃዎች ዙርያ ከስምምነት ላይ መድረሳቸውን አስታወቀዋል።
ሶስቱ አገራት ይህን ያስታወቁት ትናንት መስከረም 30 ቀን 2017 ዓ.ም. በአስመራ የተካሄደውን ጉባኤ ተከትሎ ባወጡት የጋራ መግለጫ ነው።
መሪዎቹ “የውስጥ እና የውጭ ተግዳሮቶችን” ለመፍታት እንዲቻል የሶማሊያን ተቋማት ለማጠናከር መስማማታቸውን የጋራ መግለጫው አመልክቷል።
እንዲሁም የአካባቢው ሀገራት ሉዓላዊነት፣ ነፃነት እና የግዛት አንድነት መከበር አስፈላጊ መሆኑን አጽንኦት ሰጥተዋል።
በኤርትራው ፕሬዝዳንት ኢሳያስ አፈወርቂ ጋባዥነት ለተካሄደው የሶስትዮሽ ጉባኤ የሶማሊያው ፕሬዝዳንት ሀሰን ሼክ ሞሐመድ እና የግብፁ ፕሬዝዳንት አብዱልፈታህ ኤልሲሲ መስከረም 29 እና 30፣ 2017 ዓ.ም. ተከታትለው አስመራ ገብተዋል።
የሶስትዮሽ ውይይቱ የተካሄደው ኢትዮጵያ ከሶማሊላንድ ጋር የተፈራረመችውን የባሕር በር ስምምነት ተከትሎ የአፍሪካ ቀንድ ከፍተኛ ውጥረት ውስጥ በገባበት ወቅት ነው።
ግብፅ በቅርቡ ከባድ የጦር መሳሪያዎችን ጨምሮ ወታደራዊ ተሽከርካሪዎችን ወደ ሶማሊያ መላኳ ሁኔታውን አወሳስቦታል።
በነሐሴ ወር 2016 ዓ.ም. በግብፅ እና በሶማሊያ መካከል የተፈረመው የመከላከያ ስምምነት አካል የሆነው ይህ ድጋፍ በኢትዮጵያ እና በሶማሌላንድ ላይ ስጋት ፈጥሯል።
በተጨማሪም በመግለጫው መሰረት “የሶስትዮች ጉባኤው በሱዳን ስላለው ቀውስ እና ቀጣናዊ ውጤቶቹ እንዲሁም በቀይ ባህር አከባቢ ባሉ ሃገራት መንግስታት እና በባብ አል-ማንዳብ የባህር ዳርቻ መካከል ያለውን የፀጥታ እና የትብብር ጉዳዮችን ጨምሮ በርካታ ጉዳዮች ላይ” መክሯል።
ስብሰባው በሁሉም መስኮች ትብብር ለማድረግ “የኤርትራ፣ ግብፅ እና ሶማሊያ የሶስትዮሽ የውጭ ጉዳይ ሚኒስትሮችኮሚቴ ለማቋቋም ከስምምነት ላይ በመድረስ ተጠናቋል ተብሏል። አስ