ዜና፡ በጸጥታው ምክር ቤት የሶማሊያው ልዩ መልዕክተኛ ማብራሪያ በሀሰት የተሞላ ነው ስትል ኢትዮጵያ አስተባበለች

አዲስ አበባ፣ የካቲት 14/2016 ዓ.ም፡- ከቀናት በፊት በጸጥታው ምክር ቤት ተገኝተው የመንግስታቸውን አቋም ያንጸባረቁት የሶማሊያው ልዩ መልዕክተኛ ንግግር በሀሰት የተሞላ ነው ስትል ኢትዮጵያ አስተባበለች።

የኢትዮጵያ መንግስት ኒውዮርክ በሚገኘው የመንግስታቱ ድርጅት ቋሚ መልዕክተኛ ጽ/ቤት በኩል ባወጣው ጋዜጣዊ መግለጫው እንዳስታወቀው የሶማሊያው ልዩ መልዕክተኛ ንግግር አሳዝኖኛል ብሏል።

የሶማሊያው ልዩ መልዕክተኛ ንግግር ልቅ የሆነ የሀሰት መረጃ ላይ የተመሰረተ ከመሆኑ ባለፈ የሶማሊያ መንግስት ባለስለጣናት በኢትዮጵያ ላይ እየነዙት ያለው መሰረት የሌለው ውንጀላ ተቀጽላ ነው ሲል ተችቷል።

የኢትዮጵያ መንግስት በኒውዮርክ ጽ/ቤቱ ባወጣው መግለጫው በኢትዮጵያ እና በሶማሊያ ሕዝቦች መካከል ያለውን የወንድማማችነት ትስስር በማክበር የሶማሊያ ተወካይ የተከተሉትን መንገድ እንደማይከተል አመላክቷል።

ከሶማሊላንድ ጋር የተደረሰው ስምምነት አለም አቀፍ አካሄድን የተከተለ ነው፣ ሌሎች ሀገራት ወደ ባህር በር ለመቅረብ የሚፈጽሙት የመሬት ኪራይ ጋር የተመሳሰለ ነው ሲል መግለጫው አትቷል።

በሶማሊያ በአሁኑ ወቅት የሚታየው አንጻራዊ የሆነ ሁለንተናዊ መሻሻል በሺዎች በሚቆጠሩ ኢትዮጵያውያን መስዋዕትነት የከፈሉበት የጸረ ሽብር ስራ ውጤት ነው ሲል ገልጿል።

የተባበሩት መንግስታት ድርጅት የጸጥታው ምክር ቤት የካቲት 11 ቀን 2016 ዓ.ም ባካሄደው ስብሰባ በኢትዮጵያ እና በሶማሊያ መካከል በተፈጠረው ውጥረት ዙሪያ መወያየቱን መዘገባችን ይታወሳል።

በምክር ቤቱ ተገኝተው የመንግስታቸውን አቋም ያሰሙት በጸጥታው ምክር ቤት የሶማሊያ አምባሳደር የኢትዮጵያ መንግስት የባህር በር ለማግኘት ሲል ከሶማሊላንድ ጋር የፈጸመው ስምምነት ቀጠናውን ብቻ ሳይሆን አለምአቀፍ ቅቡል የሆነውን የነጻ ሀገራት ሉአላዊነትን እና ነጻነትን የሚጻረር ነው ሲሉ መግለጻቸው በዘገባው ተካቷል።

ኢትዮጵያ በሶማሊያ ምድር ላይ የጦር ሰፈር የምትመሰርት ከሆነ በግልጽ በሶማሊያ እና በህዝቧ ላይ ጦርነት እንዳወጀች የሚቆጠር ነው ብለዋል። የአዲትዮጵያ ተግባር በአልሸባብ ላይ በሶስት አስርት አመታት ጥረት ያገኘነውን ስኬት በመቀልበስ ለሚያደርገው ጥረት አጋዥ ይሆነዋል ሲሉ አስጠንቅቀዋል።

የዚህ አይነት ተግባር ውጤት ውስብስበ የብሔሮች ስብስብ በሆነችው ኢትዮጵያ ላይ አለመረጋጋት ሊያስከትል ይችላል ሲሉ ገልጸዋል። በቀጠናው የሚንቀሳቀሱ የመገንጠል ሀሳብ የሚያቀነቅኑ የብሔር ቡድኖች እንዲያብቡ ምቹ ሁኔታን የሚፈጥር ነው ብለዋል።

የምክር ቤቱ አባላት በኢትዮጵያ እና በሶማሊያ መካከል የተፈጠረው አለመግባባት እንዳሳሰባቸው እና ሁለቱ አገራት ጉዳዩን በውይይት እንዲፈቱት ጥሪ አቅርበዋል። አስ

Exit mobile version