ዜናፖለቲካ

ዜና፡ ኢሰመኮ የሐሰት ሪፖርት አውጥቷል ሲል የትግራይ ግዜያዊ አስተዳደር ኮነነ

አዲስ አበባ፣ ጥቅምት 16/2016 .ም፡ የኢትዮጵያ ሰብአዊ መብት ኮሚሽን የሀገር ውስጥ ተፈናቃዮችን አስመልክቶ ባወጣው ሁለት ሪፖርቶች በትግራይ ክልል ከቀያቸው ተፈናቅለው የነበሩ የክልሉ ነዋሪዎች ወደ መኖሪያቸው እየተመለሱ ነው ሲል ያወጣው ሪፖርት ፍጹም ሐሰት ነው ሲል የትግራይ ክልል ግዜያዊ አስተዳደር ባወጣው መግለጫ ኮንኗል።

ኮሚሽኑ በበኩሉ በጉዳዩ ዙሪያ በፌስቡክገጹ ባወጣው መረጃ ጥናቱን በሚያካሂድበት ወቅት ትግራይ አለመካተቷን አስታውቆ በሪፖርቱ ላይ ትግራይ መካተቷ የተሳሳተ መረጃ መሆኑን በመግለጽ መረጃውን ለማጥራት ከግዜያዊ አስተዳደሩ በመተባበር እንደሚሰራ ጠቁሟል።

በተያያዘ መረጃ የኢትዮጵያ ሰብአዊ መብት ኮሚሽን የሀገር ውስጥ ተፈናቃዮችን አስመልክቶ ባወጣው ሁለተኛው ሪፖርት በትግራይ ተካሂዶ በነበረው ጦርነት ወቅት ከቀያቸው ተፈናቅለው የነበሩ ዜጎች ወደ መኖሪያቸው እየተመለሱ ነው በሚል ያወጣሁት ሪፖርት የአማራ እና አፋር ክልልን እንጂ የትግራይ ክልልን ተፈናቃዮች አያካትትም ሲል ዛሬ ጥቅምት 16 ቀን 2016 ዓ.ም ይፋዊ ፌስቡክ ገጹ ባጋራው መረጃ አስታውቋል።

የክልሉ ጊዜያዊ አስተዳደር፣ በሚሊዮን የሚቆጠሩ የትግራይ ተወላጆች ከቤት ንብረታቸው ተፈናቅለው በአስከፊ ሁኔታ ላይ በሚገኙበት ወቅት እና የግዜያዊ አስተዳደሩ ተፈናቃዮች ወደ ቤታቸው እንዲመለሱ የሚል ሌት ተቀን ጥሪ ባቀርብም ምንም አይነት ምላሽ ባልተሰጠበት ሁኔታ ኮሚሽን የዚህ አይነት ሃላፊነት የጎደለው መግለጫ ማውጣቱ  ከዚህ ቀደም እንዳደረገው በትግራይ ህዝብ ላይ ማላገጡን እንደቀጠለ መሆኑን የሚያሳይ ነው ሲል ተችቷል። በተጨማሪም የጊዜያዊ አስተዳደሩ በመግለጫው ኮሚሽኑ ያወጣው ሪፖርት ሆን ብሎ አለም አቀፉን ማህበረሰብ ለማሳሳት በመሆኑ ተቀባይነት የለውም ሲል ኮንኗል።

የፌደራል መንግስቱ በሀገሪቱ የሚገኙ ተቋማት መሰል ሃላፊነት የጎደለው የተሳሳተ መረጃ ማውጣታቸው የሰላም ሂደቱ ላይ የሚኖረውን አሉታዊ ተጽእኖ ግምት ውስጥ በማስገባት አስፈላጊውን ርምጃ እንዲወስድ ሲል ጊዜያዊ አስተዳደሩ በመግለጫው አሳስቧል። አስ

ተጨማሪ አሳይ

ተዛማጅ ጽሑፎች

Back to top button