ዜናፖለቲካ
በመታየት ላይ ያለ

ዜና፡ በኢትዮጵያ የዘር ማጥፋት ወንጀል ከፍተኛ ስጋት አለ ሲሉ የመንግስታቱ ድርጅት ልዩ አማካሪ አስጠነቀቁ

አዲስ አበባ፣ መስከረም 30/2016 .ም፡ በፌደራል መንግስቱ ወታደሮች እና በሀገሪቱ በተለያዩ አከባቢዎች የሚገኙ ታጣቂዎች መካከል የቀጠለ ውጊይ እየተካሄደ መሆኑ በኢትዮጵያ አሁንም የዘር ማጥፋት እና ተያያዠ አሰቃቂ ወንጀሎች ስጋት ከፍተኛ ሁኔታ አጥልቷል ሲሉ የመንግስታቱ ድርጅት የዘር ማጥፋት መከላከል ልዩ አማካሪ ዋይሪሙ ንደሪቱ አስጠነቀቁ።

ልዩ አማካሪው ዋይሪሙ ንደሪቱ በትግራይ፣ አማራ፣ አፋር እና ኦሮምያ ስጋቱ ከፍተኛ መሆኑን እና የዘር ማጥፋት ወንጀል ለመፈጸም አስቻይ ሁኔታዎች መኖራቸውን ጠቁመዋል።

አሁንም ሀይል የተቀላቀለበት ግጭት እንደቀጠለ በመሆኑ ከአንድ አመት በፊት የተፈረመው የሰላም ስምምነቱ ባመዛኙ አልተሳካም ማለት በሚቻልበት ደረጃ ላይ ይገኛል ያሉት ልዩ አማካሪዋ ግፎች፣ የጦር ወንጀሎች እና በሰው ዘር ላይ የተቃጣ ወንጀል ደረጃ ላይ የሚመደቡ ጥፋቶች በሀገሪቱ ተፈጽመዋል ሲሉ ገልጸዋል።

ከኢትዮጵያ እየተፈጸሙ ስላሉት ወንጀሎች የተመለከቱ የሚደርሱን ሪፖርቶች እጅግ የሚረብሹ ናቸው ሲሉ የገለጹት ልዩ አማካሪዋ በአፋጣኝ ሁኔታውን ለመከላከል እርምጃ ሊወሰድ ይገባዋል ብለዋል። አለም አቀፉ ማህበረሰብ በጉዳዩ ላይ ልዩ ትኩረት እንዲሰጠው ጥሪ ማቅረብ እወዳሉ ሲሉ ገልጸዋል።

እየደረሱን ካሉ ሪፖርቶች መካከል ሙሉ ቤተሰብ ግድያ የተፈጸመባቸው ይገኛሉ ያሉት አማካሪዋ ቤተሰቦች በሚወዷቸው ወገኖቻቸው ላይ የሚፈጸምን አሰቃቂ ተግባር እንዲመለከቱም ይደረጋል፣ በተጨማሪም ሙሉ መንደር ተፈናቅሎ ቤቱን ጥሎ እንዲሰደድ ይደረጋል ሲሉ እየተፈጸመ ስላለው ግፍ አስታውቀዋል።

በአገሪቱ የዘር ማጥፋት ወንጀልና ሌሎች ጥሰቶች እንዳይከሰቱ ከአሁኑ መከላከል እንደሚያስፈልግም ልዩ አማካሪዋ አሳስበዋል። የኤርትራ ወታደሮች እና የአማራ ሚሊሻዎች በትግራይ ሴቶች ላይ የሚፈጽሙት አስከፊ ወንጀል፣ አስገድዶ መድፈር እና ወሲባዊ ጥቃት እንደቀጠለ ነው ሲሉ የገለጹት ልዩ አማካሪዋ በአማራ ክልል የአስቸኳይ ግዜ አዋጁ ከታወጀ ወዲህ በክልሉ ነዋሪዎች ላይ አስከፊ ጥቃቶች እየተፈጸሙ ለመሆናቸው አሳማኝ ማስረጃዎች አሉ ብለዋል፤ የሚፈጸሙ ጥቃቶች ባስቸኳይ እንዲቆሙም ጠይቀዋል።

የአለም አቀፉ የሰብአዊ መብት ኤክስፐርቶች በኢትዮጵያ (ICHREE) ለተባበሩት መንግስታት ድርጅት የሰብአዊ መብቶች ምክር ቤት ባቀረበው ሪፖርት በኢትዮጵያ አሁንም የጦር ወንጀል እና በሰብአዊነት ላይ የሚፈጸም ወንጀል እንደቀጠለ ነው ሲል መግለጹን ልዩ አማካሪዋ በአብነት አስቀምጠዋል። አስ

Download the First Edition of Our Quarterly Journal
ተጨማሪ አሳይ

ተዛማጅ ጽሑፎች

Back to top button