የህዝብ ተወካዮች ምክር ቤት በቀጣይ አመት ከ80 በላይ አዲስ የምክር ቤት አባላት እንደሚመጡ አስታወቀ፣ ከ700 ሚሊየን ብር በላይ በጀት ጠይቋል

አዲስ አበባ፣ ግንቦት 20/2016 ዓ.ም፡-የህዝብ ተወካዮች ምክር ቤት በቀጣይ አመት ከ80 በላይ አዲስ የምክር ቤት አባላት ስለሚመጡ ለስራ ማስኬጃ ከ700 ሚሊየን ብር በላይ በጀት እንዲጸድቅለት ጠየቀ

የህዝብ ተወካዮች ምክር ቤት በቀጣይ ዓመት 2017 ምክር ቤቱ ስራውን በይበልጥ ተደራሽ ለማድረግ ያግዘው ዘንድ ከ700 ሚሊየን ብር በላይ በጀት እንዲጸድቅለት ለፕላን፣ በጀትና ፋይናንስ ጉዳዮች ቋሚ ኮሚቴ መጠየቁ ተገለጸ።

ከጠየቀው አጠቃላይ በጀት ውስጥ የመደበኛ በጀት 554‚ ሚሊዮን 550‚ ሺህ 2 መቶ 58 እንዲሁም የካፒታል በጀት 150‚ ሚሊዮን ብር መሆኑም ተጠቁሟል።

የምክር ቤቱ የበጀት ጥያቄ የተጋነነ እንዳይሆን አሳማኝ እና ምክንያታዊ በመሆነ መልኩ መቅረብ እንዳለበት በሕዝብ ተወካዮች ምክር ቤት የፕላን፣ በጀትና ፋይናንስ ጉዳዮች ቋሚ ኮሚቴ አሳስቧል።

የስልጠና፣ የማሽነሪዎችና የጥገና ወጪዎች እንዲሁም የካፒታል በጀት ምን ያህል ወጪ ይጠይቃል የሚለው በትክክል እና ግልጽ በሆነ መንገድ መቀመጥ እንዳለበት የቋሚ ኮሚቴው አቶ ደሳለኝ ወዳጄ አመላክተዋል፡፡

የቀረበው በጀት የተጋነነ እንዳልሆነ እና በቀጣይ ዓመት ወደ ምክር ቤቱ የሚመጡ ከ80 በላይ አዲስ የምክር ቤት አባላት የነሱንም የደመወዝ እና የፕሮቶኮል ወጪ ታሳቢ ማድረግ እንደሚገባ የሕዝብ ተወካዮች ምክር ቤት ጽ/ቤት ዋና ጸሐፊ ዶክተር ምስራቅ መኮንን አስረድተዋል፡፡

በጀቱ የሀገር ውስጥ እና የውጭ ሀገራት የአውሮፕላን ትኬት እና የስልጠና ወጪዎችን እንዲሁም የምክር ቤት አባላት የመስክ ስራ ጋር በተያያዘ የነዳጅ ወጪዎችን ታሳቢ ማድረግ እንዳለበትም ዶ/ር ምስራቅ አክለዋል፡፡

የቋሚ ኮሚቴው አባላት አያይዘውም የምክር ቤቱን ስራ በይበልጥ ለህዝብ ተደራሽ ለማደረግ የምክር ቤቱ ማህበራዊ ሚዲያ ወደ ቴሌቪዥን ማሳደግ አልተቻለም የሚል ጥያቄ የጽ/ቤት አመራሮችን ጠይቀዋል፡፡

የምክር ቤቱ ጽ/ቤት ሙያዊ ዘርፍ ምክትል ዋና ጸሐፊ ንጉሤ መሸሻ (ዶ/ር) የምክር ቤቱን ቴሌቭዥን ከማስጀመር ጋር በተያያዘ ከ2 መቶ አስከ 4 መቶ ሚሊዮን ወጪ የሚጠይቅ በመሆኑ ወደስራ መግባት እንዳልተቻለ አስረድተው፤ በቀጣይ ካሜራን ጨምሮ አስፈላጊ ማቴሪያሎች ከተሟሉ የኦን ላይን ሚዲያ ለማስጀመር እንደሚሰሩ መግለጻቸውን ከምክር ቤቱ ያገኘነው መረጃ ያሳያል። አስ

Exit mobile version