ርዕሰ አንቀፅ
በመታየት ላይ ያለ

ርዕስ አንቀጽ: በኦሮምያ እና አማራ ክልሎች የተፈጠሩ ግጭቶችን በድርድር ማስቆም የምርጫ ጉዳይ ሳይሆን የሀገሪቱን ብሔራዊ ደህንነት ማስጠበቅ ነው

አለም አቀፉ ማህበረሰብ ትኩረት ባይሰጠውም በታንዛንያ የተካሄደው የፌደራል መንግስቱ እና የኦሮሞ ነጻነት ሰራዊት የሰላም ድርድር በኦሮምያ ክልል ብቻ ሳይሆን በመላ ሀገሪቱ ለብዙዎች ተስፋ የሰጠ ነበር። ብዙዎች የበርካታ ሰዎችን ህይወት እየቀጠፈ ያለው ጦርነት እንዲያበቃ ያስችላል በሚል ድርድሩ አወንታዊ ውጤት ይዞ ይመጣል ብለው ጠብቀውም ነበር።  

የኦሮምያ ክልል የሚገኙም ይሁን በሁለቱም ተፋላሚ ሀይሎች በኩል የሚገኙ በሚሊዮን የሚቆጠሩ ሰዎች ታማኝ በሆነ ሶስተኛ ወገን አደራዳሪዎች ባሉበት የሁለቱም ከፍተኛ ወታደራዊ አመራሮች ፊት ለፊት ተገናኝተው መምከራቸው ተስፋ እንዲሰንቁ አድርጓል።

ነገር ግን ሚሊዮኖችን ባሳዘነ መልኩ በታንዛንያዋ ዋና ከተማ ዳሬሰላም የተካሄደው ድርድር ከሁለት ሳምንታት በኋላ ሳይሳካ ተጠናቀቀ። ከአምስ አመታት በፊት ከፍተኛ ጉዳት እያስከተለ የሚገኘውን ጦርነት እንዲያበቃ ለማስቻል የሚያግዝ እና ድርድሩ እንደሚቀጥል ምንም ፍንጭ የሚሰጥ መግለጫ በድርድሩ መጠናቀቂያ ላይ አለመስጠታቸው አሁንም ስጋቱ እንዲቀጥል አድርጓል።

ወሳኝ እርምጃዎች ካልተወሰዱ በስተቀር በኦሮምያ የሚካሄደው የእርስ በርስ ጦርነት ላልታወቀ ግዜ የሚቀጥል መሆኑ ግልጽ ነው። መንግስትም ይሁን የኦሮሞ ነጻነት ሰራዊት ጦርነቱን አንዱ አንዱን ሙሉ በሙሉ በማሸነፍ የማጠናቀቅ እድል የላቸውም።

በድርድሩ አለመሳካት ዙሪያ ሁለቱም ወገኖች እርስ በርስ በመወነጃጀል ላይ ይገኛሉ። መንግስት ለድርድሩ አለመሳካት የኦሮሞ ነጻነት ሰራዊትን ተጠያቂ በማድረግ ላይ ሲሆን ቡድኑ ግትር አቋም አንጸባርቋል፣ ወቅቱን የጠበቁ ጥያቄዎች ይዞ መቅረብ ተስኖታል ሲል ይወነጅላል። የኦሮሞ ነጻነት ሰራዊት በበኩሉ ለድርድሩ አለመሳካት ተጠያቂው መንግስት ነው ሲል የተቸ ሲሆን በአንገብጋቢ ጉዳዮች ዙሪያ ለመደራደር ከመፈለግ ይልቅ የሰራዊቱን አመራሮች በጥቅማ ጥቅም ለመደለል ሞክሯል ሲል ኮንኗል።

ድርድሩ እየተካሄደ በነበረበት ወቅት መንግስት በኦሮሞ ነጻነት ሰራዊት ላይ ይነዛ የነበረው ፕሮፓጋንዳ ለድርድሩ ምን ያክል ቁርጠኛ ነው የሚል ጥርጣሬ እንዲፈጥር አድርጓል። ድርድሩ ያለስምምነት እንደተጠናቀቀም ያወጣቸው የነበሩ ተንኳሽ መግለጫዎች የሚያሳጡት ነበሩ። ከዚህ ባለፈ ድርድሩ ያለስምምነት እንደተጠናቀቀ ያካሄደው ወታደራዊ ዘመቻ በዜጎች ላይ ያደረሰው ጉዳት እና ሞት ከፍተኛ ነው።

ድርድሩ ከተጠናቀቀ በኋላ ባሉት ሁለት ሳምንታት በኦሮምያ በአርሲ፣ ሆሮ ጉድሩ፣ ምዕራብ ወለጋ እና ቡኖ በደሌ ዞን በትንሹ 100 ሰዎች ተገድለዋል። ከግድያዎቹ ጋር በተያያዘ አንዱ አንዱን ተጠያቂ በማድረግ መወነጃጀሉ እንደተጠበቀ ሁኖ።

Download the First Edition of Our Quarterly Journal

የተራዘመ ጦርነት ምን እንደሚያስከትል ይህ በቂ ማሳያ ነው፣ የንጹሃንን መከራ ከማብዛት እና እየተንገዳገደ ያለውን የሀገሪቱን ኢኮኖሚ ከማድቀቅ ያለፈ ውጤት አይኖረውም። ወሳኝ እርምጃዎች ካልተወሰዱ በስተቀር በኦሮምያ የሚካሄደው የእርስ በርስ ጦርነት ላልታወቀ ግዜ የሚቀጥል መሆኑ ግልጽ ነው። መንግስትም ይሁን የኦሮሞ ነጻነት ሰራዊት ጦርነቱን አንዱ አንዱን ሙሉ በሙሉ በማሸነፍ የማጠናቀቅ እድል የላቸውም።  

በኦሮምያ ክልል በመካሄድ ላይ ላለው ጦርነት ሰላማዊ መፍትሔ አለማምጣት ማለት በአማራ ክልል በመንግስት እና በፋኖ ታጣቂ ሀይሎች መካከል የሚካሄደውን ጦርነት የተራዘመ እንዲሆን የሚኖረው ተጽእኖ ከፍተኛ ነው።

ሁለቱም ተፋላሚ ሀይሎች ይህንን እውነት አለመረዳታቸው እና አስፈላጊ የሆኑ በድርድር ሰጥቶ የመቀበል መርሆችን ተግባራዊ ካላደረጉ ዳፋው ለኦሮሞ ህዝብ ብቻ ሳይሆን ለሀገሪቱ ብሔራዊ ደህንነትም አደጋ የሚያስከትል ነው።

በተፈጥሮ እና በኢኮኖሚ አደጋ ላይ ያለች እንዲሁም በወረርሽኝ ምክንያት ቸግር ላይ የወደቀችን ሀገር በሰው ሰራሽ ጦርነትን በሰላማዊ መንገድ መፍታት የምርጫ ጉዳይ ሳይሆን የግድ አስፈላጊዋ ነው።

በኦሮምያ ክልል በመካሄድ ላይ ላለው ጦርነት ሰላማዊ መፍትሔ አለማምጣት ማለት በአማራ ክልል በመንግስት እና በፋኖ ታጣቂ ሀይሎች መካከል የሚካሄደውን ጦርነት የተራዘመ እንዲሆን የሚኖረው ተጽእኖ ከፍተኛ ነው። ባለፉት ስምንት ወራት ብቻ ወታደራዊ ግጭቱ ሊገለጽ የማይችል ውድመት እና ሞት በክልሉ ላይ አድርሷል።  

በአማራ ክልል ባሳለፍነው አመት ሚያዚያ ወር ላይ ግጭት ከተጀመረበት እለት አንስቶ መንግስት በተደጋጋሚ የክልሉን አብዘሃኛውን አከባቢ ሰላማዊ እና የተረጋጋ አድርጊያለሁ ብሎ ቢገልጽም የፋኖ ታጣቂዎች ከፍተኛ የሆነ ችግር እየፈጠሩበት መሆኑ በግልጽ የሚታይ ነው።

ታጣቂ ቡድኑን መሳሪያ ለማስፈታት በሚያደርገው ጥረት በከባድ መሳሪያዎች እና በድሮን የታገዘ ጥቃት በመፈጸም ላይ ይገኛል። ይህም ከአንድ አመት በፊት በሌላ ጦርነት ሳቢያ ችግር ላይ የወደቀውን የክልሉ ህዝብ እና ንብረት ላይ እያደረሰ ያለው ጉዳት ከፍተኛ ነው። በርካታ ንጹሃን ተገድለዋል፣ ንብረት ወድሟል።

በቅርቡ በደቡብ ወሎ ደላንታ ወረዳ የመድሃኒት ግብአቶችን ይዞ በመጓዝ ላይ በነበረ አንቡላንስ ላይ በተፈጸመው የድሮን ጥቃት አምስት ንጹሃን ተገድለዋል፣ አንቡላንሱም ወደ ስብርባሪ ተቀይሯል፤ ይህ ስለክልሉ ነባራዊ ሁኔታ ትልቅ ማሳያ ነው።

በህዳር ወር የተባበሩት መንግስታት ድርጅት የሰብአዊ ጉዳዮች ቢሮ ኦቻ ይፋ ያደረገው መረጃ እንደሚያሳየው በክልሉ በትምህርት ቤት እና በአውቶብስ መናሃሪያ ላይ በድሮን በተፈጸመ ጥቃት 20 ንጹሃን ተገድለዋል። ይህም በግጭት ሰበብ በክልሉ እየተፈጸመ ላለው የሰብአዊ መብት ጥሰት ማሳያ ነው።

ሌላኛው ብዙም ያልተነገረለት የክልሉ ነባራዊ ሁኔታ ደግሞ የመንገዶች መዘጋት ነው፤ በግጭቱ ሳቢያ መንገዶች መዘጋታቸው የሰብአዊ ረድኤት በወቅቱ እንዳይዳረስ እንቅፋት ከመሆኑ ባሻገር ለክልሉ አርሶ አደር የሚያስፈልጉ የግብርና ግብአቶች እንዳይደርሱት አድርጓል።  

በዚህ ብቻ ሳያበቃ በጥቅምት ወር መጀመሪያ አከባቢ የክልሉ የትምህርት ቢሮ ይፋ ያደረገው ሪፖርት እንደሚያሳየው ስድስት ሚሊየን ከሚሆኑት የክልሉ ተማሪዎች ውስጥ ሶስት ነጥብ ዘጠኝ ሚሊየን የሚሆኑት በትምህርት ገበታቸው ላይ አይገኙም። በግጭቱ ምክንያት ትምህርታቸውን መከታተል ሳይችሉ ቀርተዋል።

በኦሮምያ እና በአማራ ክልል ያለው ግጭት የሚኖረው ተጽእኖ ከንጹሃን ስቃይ እና መከራ ያለፈ ነው፣ በሀገሪቱ ብሔራዊ ደህንነት ላይ አደጋ የደቀነ ነው።

ምንም እንኳ ግጭቱ በሰላማዊ መንገድ እንዲፈታ እንደ አብን ያሉ የሀገር ውስጥ አካላት እና ከአሜሪካ መንግስት በኩል በተደጋጋሚ ጥሪ ቢቀርብም ሁለቱም ወገኖች ያሳዩት ዝግጁነት የለም።

በቅርቡ የአሜሪካ የታችኛው የህግ አውጪ ምክር ቤት ኮንግረስ የውጭ ጉዳይ ኮሚቴ የአፍሪካ ጉዳዮች ንዑስ ኮሚቴ ባካሄደው ፕሮግራም ላይ እንደተደመጠው በኦሮምያ እና በአማራ ክልል ያለው ግጭት የሚኖረው ተጽእኖ ከንጹሃን ስቃይ እና መከራ ያለፈ ነው፣ በሀገሪቱ ብሔራዊ ደህንነት ላይ አደጋ የደቀነ ነው።

በቅርቡ በፌደራል መንግስት እና በኦሮሞ ነጻነት ሰራዊት መካከል በተካሄደው የሰላም ድርድር ላይ ተሳታፊ የነበሩት የአሜሪካ መንግስት የአፍሪካ ቀንድ ልዩ መልዕክተኛ ማይክ ሀመር ፍቃደኛ ከሆኑ የፋኖ ሚሊሻዎችን እና መንግስትን ለማደራደር ዝግጁ ነን ማለታቸው ይታወቃል። ዲፕሎማቱ በተጨማሪም ሀገራቸው የኦሮምያ ክልልን ችግር በሰላማዊ መንገድ እልባት እንዲያገኝ ለማስቻል የምታደርገውን ድጋፍ አሁንም ቁርጠኛ መሆኗን አስታውቀዋል።

ሳይዘገይ ይህንን እድል በመጠቀም ችግሮቹን በሰላማዊ መንገድ ለመፍታት ግዜው አሁን ነው፣ የጠመንጃ ድምጽ ይብቃ፣ የኢትዮጵያ ህዝብ የሚገባውን እፎይታ ያግኝ። አስ

ተጨማሪ አሳይ
Back to top button