አዲስ አበባ፣ መስከረም 11/ 2016 ዓ.ም፡- በትግራይ ምስራቃዊ ዞን አፅቢ ወረዳ ስር በሚገኙ ዘጠኝ ቀበሌዎች ባጋጠመው የድርቅ አደጋ ከ100,000 በላይ ነዋሪዎች ለአደጋ መጋለጣቸውን የወረዳው ዋና አስተዳዳሪ እና ነዋሪዎች ገለፁ፡፡
የወረዳዋ ዋና አስተዳዳሪ አቶ መዝገበ ግርማይ በክረምቱ ወቅት በወረዳዋ በሚገኙ 12 ቀበሌዎች 8445 ሄክታር መሬት በተለያዩ አዝርእቶች ተሸፍኖ የነበረ ቢሆንም ባጋጠመው የዝናብ እጥረት ምክንያት በዘጠኝ ቀበሌዎች ላይ የሚገኘውን 7310 ሄክታር ታራሽ መሬት በከባድ ድርቅ ተመቷል ሲሉ ለድምፂ ወያኔ ተናግረዋል።
በዚህም ምክንያት ከመቶ ሺህ በላይ ነዋሪዎች እና ከሁለት መቶ ሺህ በላይ እንስሳት ለምግብ እና ወሃ እጥረት ተጋልጠው በአደጋ ውስጥ ናቸው ብለዋል፡፡
የአከባቢው ነዋሪዎች በበኩላቸው ለሚዲያው በሰጡት አስተያያት በክረምቱ በቂ ዝናብ መዝነብ ባለመቻሉ ከፍተኛ ድርቅ አደጋ በመከሰቱ እንስሳት እየሞቱ መሆናቸውን ገልፀዋል።
ምንም እንኳ አንዴ ሁለቴ በዘነበው ዝናብ አርሶ አደሩ ሰብል ለመዝራት ጥረት አድርጎ ቢሆንም ዝናቡ በመቋረጡ የተዘራው አዝርእት የእንስሳት ቀለብ እንዲሆን መደረጉን የተናገሩት ነዋሪዎቹ ሰውም ሆነ እንስሳቱ ለከፍተኛ የድርቅ አደጋ መጋለጣቸውን እና የከፋ እልቂት እንዳይከሰት ስጋት ውስጥ መውደቃቸውን ተናግረዋል።
በመሆኑም የትግራይ ጊዚያዊ አስተዳደር፣ ፌደራል መንግስት ሆነ ለጋሽ ድርጅቶች እና በውጭ ሃገራት የሚገኙ የአፅቢ ወረዳ ተወላጆች እና ወዳጆች አስፈላጊውን ድጋፍ እንዲያደርጉ ነዋሪዎቹ እና አስተዳዳሪው ጥሪ ማቅረባቸው በዘገባው ተካቷል፡፡
በተመሳሳይ መልኩ በሰሜን ጎንደር ዞን በተከሰተው ድርቅ ምክንያት ድጋፍ ከሚያስፈልጋቸው 452 ሺህ 851 ሰዎች ውስጥ ከ200 ሺህ በላይ የሚሆኑት አስቸኳይ የምግብ ድጋፍ እንደሚያስፈልጋቸው የመንግስት ሚዲያዎች ዘግበዋል፡፡ የሰሜን ጎንደር ዞን ኮሙኒኬሽን መምሪያ ሀላፊ ይርዳው ሲሳይ ለፋና እንደገለጹት በዞኑ በተከሰተው ድርቅ ምክንያት 19 ሺህ 174 ሄክታር መሬት ላይ የነበረ ማሳ ከጥቅም ውጭ ሆኗል፡፡ በበየዳ፣ ጠለምትና ጃናሞራ 4 ሺህ 88 ሰዎች አካባቢያቸውን ለቀው መሄዳቸውንም አክለው ተናግረዋል፡፡አስ