አዲስ አበባ፣ ጥቅምት 9/2016 ዓ.ም:- በኦሮሚያ ክልል ሰሜን ሸዋ ዞን መንግስት “ሸኔ” ብሎ የሚጠራው ኦሮሞ ነጻነት ሰራዊት (ኦነስ) ታጣቂዎች ትላንት ጥቅምት 9/2016 ዓ.ም የኢስት ሲሚንቶ ፋብሪካ ስራተኞች የሆኑ የቻይና ዜጎችን አግተው መውሰዳቸውን ነዋሪዎች ለአዲስ ስታንዳርድ ተናገሩ።
ስሙ እንዲጠቀስ ያልፈለገ የግራር ጃርሶ ወረዳ ፊቼ ከተማ ነዋሪ የኦነሰ ታጣቂዎች ትላንት ጠዋት በዳጋም ወረዳ ከሀምቢሶ ከተማ በ5 ኪ.ሜ ርቀት ላይ የሚገኘውን ኢስት ሲሚንቶ ፉብሪካ በመቆጣጠር በቁጥር ያልታወቁ የቻይና ዜጎችን አግተው ወስደዋል ሲል ለአዲስ ስታንዳርድ ገልጿል።
እንደ ነዋሪው ገለፃ ታጣቂዎቹ ፊቼ ከተማን በቁጥጥራቸው ስር ለማዋል በማሰብ ጋረ ሹሂ በሚባል ቦታ ላይ ከመንግስት ጸጥታ ሀይሎች ጋር ረዘም ያለና ከፍተኛ ውጊያ አድርገዋል። በዚህም ሳቢያ የመንግስት አካል በስተላለፈው ትዕዛዝ አገልግሎት ሰጭ ተቋማትና ትምህርት ቤቶች ተዘግተው መዋላቸውን ነዋሪው ተነግሯል።
” ትላንት ጠዋት ታጣቂዎቹ መጥተው ፋብሪካውን ተቆጣጥረው የቻይና ዜጎችን ከወሰዱ በኋል እስከ 8:00 ከፍተኛ ውጊያ ተደርጓል” ሲል አስረድቷል።
ለሰዓታት ከቆየው ግጭት በኋል የኦነስ ታጣቂዎች ወደ ኋላ በማፈግፈግ ወደ ጫካ ሲገቡ ግጭቱ መርገቡን ነዋሪው አስረድቷል። ነገር ግን ታጣቂዎቹ ወደ ጫካ ያፈገፈጉት የወሰዷቸውን የቻይና ዜጎች ይዘው መሆኑን አክሏል።
ሌላኛው የፊቼ ከተማ ነዋሪ በትላንትናው ዕለት ከፍተኛ ግጭት ከመካሄዱ ጋር ተያይዞ የከተማዋ ነዋሪዎች መደበኛ እንቅስቃሴያቸውን ማቋረጣቸውንና የቻይና ዜጎች በታጣቂዎቹ መወሰዳቸውን መስማቱን ለአዲስ ስታንዳርድ ገልጿል።
ነዋሪዎቹ የቻይና ዜጎቹ በታጣቂዎቹ መወሰዳቸውን ቢገልጹም ቁጥራቸውን ግን ማረጋገጥ አልቻሉም። ነገር ግን በማህበራዊ ሚዲያ ላይ ዘጠኝ መሆናቸውን የሚገልጽ መረጃ ተስተውሏል።
በዚህ ጉዳይ ላይ የዞኑን ፖሊስ መምሪያን እና የኢስት ሲሚንቶ ፋብሪካ ለማግኘት ያደረግነው ሙከራ አልተሳካም። አስ