ዜናፖለቲካ

ዜና: የኬንያ መንግስት በኦሮሞ ነጻነት ሠራዊት ላይ እያካሄደው ያለው 'ዘመቻ' ከኢትዮጵያ ጋር በመቀናጀት ነው - መረጃና ደህንነት አገልግሎት

አዲስ አበባ፣ ጥር 28/2017 ዓ.ም፡- የኬንያ ብሔራዊ ፖሊስ አገልግሎት በማርሳቢት እና ኢሲዮሎ ግዛቶች በኦሮሞ ነጻነት ሠራዊት ላይ እያካሄደ ባለው ‘ልዩ የፀጥታ ዘመቻ’ ከኢትዮጵያ ጋር በመቀናጀት ነው ሲል የብሔራዊ መረጃና ደህንነት አገልግሎት አስታወቀ።

የብሔራዊ መረጃና ደህንነት አገልግሎት ዳይሬክተር ጀነራል አምባሳደር ሬድዋን ሁሴን እና የኬንያ ብሔራዊ መረጃ አገልግሎት ዳይሬክተር ጀነራል ኑረዲን ሞሐመድ ሐጂን ጨምሮ የሁለቱ ሀገራት የጸጥታ ተቋማት ከፍተኛ አመራሮች መወያየታቸውን የአገልግሎት መሥሪያ ቤቱ የላከውን መግለጫ ዋቢ በማድረግ የመንግስት መገናኛ ብዙሃን ባሰራጩት ዘገባ አመላክተዋል።

የሁለቱ ሀገራት የደኅንነትና የጸጥታ አካላት በየድንበራቸው ውስጥ በሚገኙ የቡድኑ ካምፖች ላይ የተቀናጀ ኦፕሬሽኖች እያካሄዱ እንደሚገኙ መግለጫው ማመላከቱን ዘገባዎቹ ጠቁመዋል።

ኢትዮጵያ እና ኬንያ በቡድኑ ላይ የተቀናጀ ኦፕሬሽን ማካሄድ የጀመሩት በቀጣናዊ የጸጥታ እና ደኅንነት ጉዳዮች ዙሪያ በጋራ ለመሥራት የተፈራረሟቸውን ስምምነቶች ተግባራዊ ለማድረግ መሆኑን ዘገባዎቹ አመላክተዋል።

በሁለቱ ሀገራት ብሔራዊ ጥቅሞች ላይ ጉዳት ሊያስከትሉ የሚችሉትን ሽብርተኝነት፣ የኮንትሮባንድ ንግድ፣ ሕገ-ወጥ የሰዎች እና የመሣሪያ ዝውውርን ለከመከላከል ተግባራዊ መሆን የጀመረው የተቀናጀ ኦፕሬሽን በዋናነት በእነዚህ እንቅስቃሴዎች የሚሳተፈውን የሸኔ ታጣቂ ከሁለቱ ሀገራት ድንበሮች አካባቢ ለማስወገድ የሚረዳ እንደሆነ መረጃው አመልክቷል፡፡

በተያያዘ ዜና የኬንያ ፖሊስ ከትላንት ወዲያ ጥር 26 ቀን 2017 ዓ.ም በጀመርኩት ዘመቻ በርካታ ቡድኑ ሲጠቀምባቸው የነበሩ መሳሪያዎችን እና ንብረቶችን ማርኪያለሁ ብሏል።

በርካታ መሳሪያዎችን እና ተተኳሽ ጥይቶችን ይዣለሁ ያለው የኬንያ ፖሊስ በተጨማሪም ቡድኑ ሲጠቀምባቸው የነበሩ ንብረቶችንም ማርኪያለሁ ብሏል፤ ማርኪያቸዋለሁ ካላቸው የቡድኑ ንብረቶች መካከልም ጀረሬተር፣ የፀሃይ ሀይል መጠቀሚያ ቁሳቁሶች ይገኙበታል።

Download the First Edition of Our Quarterly Journal

ቡድኑ በኬንያ ቦረና እና በኢትዮጵያ ኦሮሞ ብሔር መካከል ያለውን የጠበቀ የቤተሰብ እና የባህል ትስስር እንደ መጠቀሚያ በመገልገል ወደ ማህበረሰቡ ዘልቆ በመግባት እና በህብረተሰቡ ውስጥ በመደበቅ ተንቀሳቅሷል ሲል የኬንያ ፖሊስ ወንጅሏል፤ በአከባቢው ማህበረሰብ ላይ ተነግሮ የማያልቅ ስቃይ እየፈጸመ ይገኛል ብሏል።

የኬንያ ፖሊስ በኦሮሞ ነፃነት ሠራዊት ላይ ‘ልዩ የፀጥታ ዘመቻ’ መጀመሩን ማስታወቁን ተከትሎ ታጣቂ ቡድኑ “ከወንጀል ድርጊቶች ጋር ግንኙነት እንደሌለው” በመግለጽ የኬንያን ሉዓላዊነትና ግዛታዊ አንድነት ሙሉ በሙሉ እንደሚያከብር መግለጹን መዘገባችን ይታወሳል።

የኦሮሞ ነፃነት ሠራዊት (ኦነሠ) ትላንት ጥር 27 ቀን 2017 ዓ.ም ባወጣው መግለጫ “ከ95 በመቶ በላይ የሚሆኑት የደቡብ እዝ ኃይላችን በኦሮሚያ ክልል ውስጥ በስፋት እንቅስቃሴ ያደርጋል” ሲል ገልጾ የተቀረው 5 በመቶ በድንበር አቅራቢያ እንደሚገኝ ጠቁሟል። ቡድኑ በመግለጫው ”ለቦረና እና ለሌሎች ወንድማማች የኬንያ ማህበረሰቦች ደህንነት እና ጸጥታ” ያለውን ቁርጠኝነት መግለጹም በዘገባው ተካቷል።  አስ

ተጨማሪ አሳይ

ተዛማጅ ጽሑፎች

Back to top button